
ባለፈው ዐርብ ታኅሣሥ 07/2015 ዓ.ም አፈና የተፈጸመባቸው የአማራ ተማሪዎች ማህበር(አተማ) ሊቀ መንበር እሸቱ ጌትነት እና መታገስ ጸጋ እስከ አሁኑ ሰዓት ድረስ አድራሻቸው አልታወቀም፤ፍርድ ቤትም አልቀረቡም፤ ወዳጅ ዘመድ ይሁን ቤተሰብ አልጠየቃቸውም፡፡ በአጠቃላይ የት፤ በማን እጅ እና በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልተቻለም፡፡ ታኅሣሥ 08/2015 ዓ.ም በባሕር ዳር ዙሪያ ወረዳ የአድማ ብተና ፖሊስ ካምፕ እንደሚገኙ ተረጋግጦ የነበረ ቢሆንም ወዲያው በመኪና ተጭነው ወደ ሰባታሚት አቅጣጫ ወዳልታወቀ ስፍራ ተወስደዋል፡፡
በመሆኑም በቀን 11/04/2015 ዓ.ም ለባሕር ዳር ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት የአካል ነጻ ማውጣት አቤቱታ ቀርቦ ለባሕር ዳር ከተማ አድማ ብተና ፖሊስ ብርጌድ መጥሪያ የተጻፈለት ቢሆንም ተቋሙ የፍርድ ቤቱን መጥሪያ ለመቀበል ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል፡፡ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽንም ስለተባሉት ሰዎች መረጃ የለኝም ብሏል፡፡
ይህም ሥርዓቱ የፍትሕ ተቋማትን የሚንቅ ፍጹም አምባገነን መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ አሁን በሀገሪቱ ላይ የሰፈነው አገዛዝ የፖለቲካ ንቃት ያለውን የማህበረሰብ ክፍል ሰብስቦ በማሰር ነውሩን ለመደበቅ የሚሞክር ከመሆኑም በላይ የሰብዓዊ መብትን የሚረግጥ እና ከፍርድ ቤት ትእዛዝ ይልቅ የፖሊስ ፍላጎት ሥርዓት ያነበረ ሆኗል፡፡
ታኅሣሥ ፲፪/ ፳፻፲፭ ዓ.ም
ከአማራ ተማሪዎች ማህበር(አተማ)



